ከእግዚአብሔር የተላከ ምልክት አይዋሽም

ከአስራ ሁለት ቀናት በፊት “ሰማያት እየተናገሩ ናቸው” በሚል ርዕስ ሥር በኦገስት 21 በአሜሪካና በካናዳ ላይ ስለሚከሰተው ታላቅ የጸሃይ ግርዶሽ የሚናገር ዜናን በማያያዝ መልእክት አስተላልፌ ነበር። መጽሐፍ ቅዱስና ታሪክ እንደሚነግረን የጸሃይና የጨረቃ ግርዶሾች እግዚአብሔር አምላከ ለህዝቦችና ለመንግስታት ሊመጣ ስለሚችል ጥፋት ከሚናገርባቸው፣ ህዝቡን ወደ ንስሃ ከሚጠራባቸውና ማስጠንቀቂያ ከሚሰጥባቸው መንገዶች አንዱ ናቸው። ባለፈው መልእክቴ ውስጥ ከአሜሪካውያን ክርስቲያኖች ወገኖቻችን ጋር በመንፈስ አንድ በመሆን ምድሪቱም ከዓመጻዋ ንስሃ እንድትገባና ወደ እግዚአብሔር እንድትመለስ እንድንጸልይ አሳስቤ ነበር።
ባለፉት ብዙ ቀናት በዜና አውታሮች እንደሰማችሁትና ከዚህ መልእክት ጋር በተያያዘው አንድ ዜና ላይ እንደምታነቡት፣ የጸሃይ ግርዶሹ ከዋለ ከአራት ቀናት በኋላ ጀምሮ ሃርቪ የተባለው ታላቅና ታሪካዊ ወጀብ ቴክሳስ ወደ ሚባለው የአሜሪካ ግዛት ገብቶ በአሜሪካ ታሪክ እስከ ዛሬ ድረስ ታይቶ የማይታወቅ ዶፍ  ለአምስት ቀናት ያህል በተከታታይ በማውረድ ከፍተኛ ጥፋት እየፈጠረ ይገኛል። http://endtimeheadlines.org/2017/08/harvey-costliest-natural-disaster-u-s-history-160-billion/
ብዙ ሰዎች በአሰቃቂ ሁኔታ ህይወታቸውን አጥተዋል፣ ቤተሰቦች ተበታትነዋል ብዙዎች ቤታቸውን ትተው ተሰደዋል፣ በብዙ መቶ ሺ የሚቆጠሩ ደግሞ ከላይ፣ ከታች፣ ከፊትና ከኋላ በከፍተኛ ጎርፍና ውሃ ሙላት ተከበዋል። የሞተው፣ የቆሰለውና የት እንዳለ የማይታወቀው ሰው ቁጥር ገና በቅል አይታወቅም። ከዚህ መልእክት ጋር በተያያዘው ሪፖርት ላይ እንደምናነበው፣ ይህ ወጀብ የፈጠረው ታላቅ ውድመት ከዚህ በፊት በአሜሪካ ታሪክ ታይቶ የማይታወቅ ነው ተብሏል። በንብረትና በአገሪቱ ኤኮኖሚ ላይ ላይ ይህ ወጀብ ያደረሰው ውድመት በ2005 እና በ2012 ተፈጥረው የነበሩት ካትሪና እና ሳንዲ የተባሉት ሁለት ታላላቅ ወጀቦች በድምር ከፈጠሩት ውድመት እንደሚበልጥና የአሜሪካንንም የዓመት ኢኮኖሚ (GDP) በ ነጥብ ስምንት ከመቶ እንደሚጎዳው ተዘግቦአል።
ወጀብ፣ ማእበል፣ ድርቅ፣ የአየር ንብረት መዛባትና ሌሎችም የተፈጥሮ አደጋዎች በየጊዜው የሚከሰቱ ናቸው ቢሉንም፣ ሁሉም ነገር የሚሆነው በአጋጣሚ ብቻ ነው የሚለው ድምዳሜ ግን እግዚአብሔርን የሚያምኑ ሰዎች በቀላሉ የሚቀበሉት አይደለም። ከላይ የተጠቀሰውን ታላቅ ወጀብ ስናስብ እጅግ የሚያስገርመው ደግሞ ከዚያው ከቴክሳስ ግዛት ብዙም ሳይርቅ የሚገኘው የደቡባዊ ካሊፎርኒያ ግዛት በበኩሉ እንደ እሳት በሚያቃጥል ሙቀትና በከፍተኛ ድርቅ እየተመታ መሆኑ ነው። ሊሰማ ለሚወድ ሁሉ ጥፋት ከመምጣቱ በፊት እግዚአብሔር በአንድም በሌላም መንገድ ደግሞና ደጋግሞ ይናገራል። በተለይም ደግሞ በከተማዎችና በአገር ላይ የሚመጣ ጥፋት እንዲሁ በአጋጣሚ የሚሆን አይደለም። ትንቢተ አሞጽ ምዕ 3 ቁ 6፣ መዝሙረ ዳዊት ምዕ 127 ቁ 1-2። የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ዳግም ምጽዓት እየተቃረበ በመጣ ቁጥርም ማእበሉና ወጀቡ ይበረታል፣ የመሬት መንቀጥቀጥ፣ የእሳተ ገሞራ ፍንዳታ፣ ድርቅ፣ ረሃብ፣ ቸነፈር፣ ጦርነትና ሁከት በምድር ሁሉ እየበዛ እንደሚሄድ በማቴዎስ ወንጌል ምእራፍ 24፣ በሉቃስ ወንጌል ምዕራፍ 21፣ በማርቆስ ወንጌል ምዕራፍ 13 እና በሌሎችም ስፍራዎች መጽሐፍ ቅዱስ ይናገራል።  የኖህ ዘመንን ዝናብ በሚመስል ታሪካዊ ዝናብ ስፋቱ ከ500 ኪሎ ሜትር በላይ የሆነ የበረሃማውን የቴክሳስን ግዛት በማጥለቅለቅና ከአሜሪካ ታላላቅ ከተሞች በአራተኛነት ደረጃ ላይ ያለችውን የሂውስተንን ከተማ ያንበረከከው ሃሪኬን ሃርቪ የፈጠረውን ጉዳት ስናስብ፣ ይህ አደጋ ከመፈጠሩ ከራት ቀናት በፊት የነበረውን የሰማያትን ማስጠንቀቂያ እናስታውስ። በዚያን ቀን ብዙ ሰዎች ግርዶሹን እንደ ማስጠንቀቂያ ከመውሰድ ይልቅ፣ ድግሶችን በማዘጋጀት አሸሸ ገዳሚ ይሉ እንደነበር በሰፊው ተዘግቧል። እኛም ለየራሳችን ከተማዎች፣ ለወገኖቻችን፣ ለያለንባቸው አገሮችም እንጸልይ። በስሙ የተጠራን ህዝቡ በፊቱ ወድቀን ንስሃ ብንገባና ከኃጢዓታችንም ሁሉ ብንመለስ እግዚአብሔር በደላቸንን ሁሉ  ይቅር እንደሚልና ያለንባቸውን ከተማዎች፣ መንደሮች፣ ማህበረሰቦችና አገሮች እንደሚፈውስ መጽሐፍ ቅዱስ ይናገራል። 2ኛ ዜና 7፡14 ሰማያትም፣ የምድር ኃይላትም እየተናገሩ ናቸው። የሚሰማ ጆሮንና የሚመለስ ልብን እግዚአብሔር ለሁላችንም ይስጠን። ወንድማችሁ ዶ/ር በፈቃዱ አድማሱ።


የሰው ዘር ዛሬ እንኳን ያልደረሰበት የሂሳብ እውቀት ከዛሬ 3700 ዓመታት በፊት በምድር እንደነበረ ማስረጃ ቀረበ

የሰው ዘር ዛሬ እንኳን ያልደረሰበት የሂሳብ እውቀት ከዛሬ 3700 ዓመታት በፊት በምድር ላይ እንደነበረ ማስረጃ ቀረበ
ከ 17ኛውና 18ኛው ክፍለ ዘመን ጀምሮ በየትምህርት ቤቱና በየዩኒቨርሲቲው በሚሰጡት ትምህርቶች ውስጥ ቀስ በቀስ ስር በመስደድ የገቡት፣ በሳይንስና በእድገት ስም የአጋንንትን ትምህርት የሚያራምዱ እውቀቶች ዛሬ የሰው ልጅ ያለበት መንፈሳዊ፣ ሞራላዊ፣ ኤኮኖሚያዊና ማህበረሰባው ምስቅልቅል ውስጥ ከትተውታል። ዘለዓለማዊ የሆነው የእግዚአብሔር ቃል የሚያስተምረውን የፍጥረትን ታሪክ ለመሻር የተነሱት እነዚህ ትምህርቶች የጥንቱ ሰው ኋላ ቀር፣ ያልተማረ፣ ውስብስብ የሆኑ ሳይንሳዊና የቴክኖሎጂ ነገሮች የማይገቡት እንደነበረ ሲያስተምሩ ምንም እፍረት አይሰማቸውም። መጽሐፍ ቅዱስ የሚያስተምረውን እውነት፣ እውነተኛውን የዓለም ታሪክና በየጊዜውም እያመለጡ የሚወጡትን የአርኪዎሎጂ ምርምር መረጃዎችን ቀረብ ብለን ከተከታተልን ግን፣ ዛሬ ብዙ ምሁራን እና የሰለጠንን ነን ብለው የሚያምኑ ሰዎች የሚናናፍሱት የዘገምታ ለውጥ (ወይም ኢቮሉሽን) የሚባለው በውሸተኞች ግብዝነት የተሰጠ የአጋንንት ትምህርት መሆኑን እንረዳለን።
የማይገለጥ የተሰወረ፣ የማይታወቅም የተከደነ የለም ተብሎ እንደተጻፈው እውነት ሁሉ በጊዜው በአደባባይ ይገለጻል። ከዚህ አጭር መልእክት ጋር ተያይዞ የሚገኘው ጽሁፍ እንደሚያሳየው፣ የተራቀቀ የሂሳብ እውቀት የመነጨው እስከ ዛሬ ድረስ ሲነገረን እንደኖረው ከግሪኮች፣ ከሮማውያን ወይም ከአውሮፓ፣ ከአሜሪካ፣ ከጃፓን ወይም ከቻይናም አይደለም። 3700 ዓመትና ከዚያም በላይ የሆናቸው ከጥንቱ የባቢሎን ግዛት የተገኙ የሸክላ ሰሌዳዎች እንደሚያመለክቱት በዚያን ዘመን የነበሩ ሰዎች ውስብስብ የሆኑ የህንጻ ቅየሳና፣ የህዋ ምርምርን እንዲሁም ሌሎች ውስብስብ የሂሳብ ስሌቶችን በማድረግ የሚሰሩ ስራዎችን ለማከናወን የሚያስችላቸው እውቀት ነበራቸው የሚለው ሃሳብ በማስረጃ እየተደገፈ መጥቷል። ታዲያ ይህን ያህል የተራቀቀ እውቀት በዚያ ከጥፋት ውሃ በፊት በነበረው ዘመን ጀምሮ ከነበረ፣ እውቀቱ በምድር ሁሉ ያልተሰራጨውና አብዛኛው የምድር ህዝብ በኋላ ቀርነት ውስጥ እስከ ዛሬ ድረስ የቆየው ለምንድን ነው የሚል ጥያቄ መነሳቱ የግድ ነው።
የአርኪዎሎጂ ምርምሩን የሚያካሂዱት ምሁራን ራሳቸው እንደሚያመለክቱት ደግሞ እነዚያ የጥንት ሰዎች ይህን የመሰለ የተራቀቀ የሂሳብ እውቀትን ቤተ ጣዖቶቻቸውንና ቤተ መንግስቶቻቸውን ለመስራት ይጠቀሙበት ነበር። ማለትም በዚያም ዘመን ቢሆን ብዙ ህዝቦች እውነተኛውን አምላክ ክደው ባእድ አማልክትን ያመልኩ ነበር። እነዚያ ባእድ አማልክት የግብጾቹ አይሲስና ኦሳይሪስ፣ የባቢሎኖቹ ማርዱክ፣ በአል፣ ቤል፣ አስታሮት፣ የግሪኮችና የሮማውያኑ አፖሎ፣ ሄርኩለስ፣ ዙስ፣ ዳያና፣ አርጤምስ፣ ቪነስ ወዘተ እነማን ነበሩ? ጠለቅ ያለ ጥናትን ለማድረግና ለዚያም የሚያስፈልገውን መስዋእትነት ለማድረግ ዝግጁ ከሆንን፣ የጥንት ህዝቦችም ሆኑ ዛሬ በምድር ሁሉ ያሉ ባእድ አማልክት የሚያመልኩ ህዝቦች የሚሰግዱት ለድንጋይና ለእንጨት ወይም ለብረት ሃውልቶች ሳይሆን በነዚያ ሃውልቶች የተመሰሉትን በኖህ ዘመን በጥፋት ውሃ የጠፉትን ረዓይት መንፈሶች (አጋንንትን) መሆኑን ልንረዳ እንችላለን። ዛሬ በሃውልትና በተለያዩ ቁሳቁስ የሚመሰሉት አጋንንት በግሪክ፣ በሮም፣ በባቢሎን፣ በፋርስ በግብጽና ሌሎችም የጥንት ግዛቶች ሲመለኩ የነበሩት እነዚያ “በጥንቱ ዘመን ስማቸው የታወቀ ኃያላን” ናቸው የሚለው ሃሳብ ዛሬ በብዙ መጽሐፍ ቅዱሳዊና ታሪካዊ መረጃዎች እየተደገፈ የመጣ ሃሳብ ነው። ይህን ዓይነት ምርምርና እውቀት ለክርስትና ህይወታችን ምን ያደርግልናል ብለን ከጠየቅን ደግሞ፣ መጽሐፍ ቅዱስ በዚህ ጉዳይ ላይ የሚናገረው ነገር አለ ወይ ብለን መመርመሩ አስፈላጊ ነው።
ኦሪት ዘፍጥረት ምእራፍ 6፣ 7 እና 8 ስለ ኖህ ዘመንና ስለ ጥፋት ውኃ የሚያስተምረንን ረጋ ብለንና በቅርብ ካጤንነው የእግዚአብሔር ልጆች (BNAI ELOHIM) የሚባሉ የሰውን ሴቶች ልጆች በወሰዱና ልጆች በወለዱላቸው ጊዜ ኔፊሊም የሚባሉ እንደተወለዱ እንመለከታለን። እነዚያ ኔፊሊም ደግሞ በዘመኑ የታወቁ ኃያላን ነበሩ። መሰረታዊው የእብራይስጡ ትርጉም ኃያላን የሚለውን ቃል “ሃጊቦሪም” ይለዋል። ይህ ቃል ደግሞ መታወቅን፣ ወኔንና ጀግናነትን ብቻ ሳይሆን እነዚያ ፍጥረታት በአካልም ከሰዎች የተለዩ ግዙፍና ጉልበተኞች እንደነበሩም ይጠቁማል። በጣም የሚያስገርመው ነገር ደግሞ፣ ልክ እነዚህ ኔፊሊም በምድር ላይ መብዛት ሲጀምሩ ነበር የሰው ልጆች ደግሞ መንገዳቸውን በምድር ላይ ያበላሹትና የእግዚአብሔርን ታላቅ ቁጣ ያነሳሱት። እውቀት በመብዛቱ ክፋትና ዓመጽ ለምን በዛ? የእውቀት መብዛት ለዓመጽ መነሳሳትና መሰራጨት አስተዋጽኦ አድርጎ ነበር ወይስ ሁለቱም በአጋጣሚ ነው የተከሰቱት? እግዚአብሔር ለሰው ልጅ የሚሰጠው እውቀትና ጥበብ ሁሉ ሰውን ወደ ጽድቅ፣ ወደ ፍቅርና ወደ እውነት እንዲሁም ወደ ዘላለም ህይወት ብቻ የሚመራ እንደሆነ መጽሐፍ ቅዱስ በግልጽ ያስተምራል። ስለዚህ የኖህን ዘመን ህዝብ ያጠፋው እውቀትና ስልጣኔ መሰል ስህተት ምንጩ እግዚአብሔር ሳይሆን በኤደን ገነት የመጀመሪያውን ውሸት ለሰው ልጅ ያስተማረው እባቡ ነው።
ከዚሁ ሃሳብ ጋር ተያይዞ ልብ ልንለው የሚገባ ነገርም አለ። ከ20ኛው ክፍለ ዘመን ጀምሮ የሰው ልጅ በአስገራሚ ፍጥነት ከፍተኛ የሳይንስና የቴክኖሎጂ እድገት ውስጥ ገብቶአል። ነገር ግን በዚሁ እጅግ ሰለጠንን በምንልበት ዘመን ደግሞ የሰው ዘር በከፍተኛ ሞራላዊ ውድቀት ውስጥ ተዘፍቆአል፣ ኤኮኖሚያዊና ማህበራዊ ቀውስ እጅግ ስር ሰድዶአል። ፈሪሃ እግዚአብሔር መሬት ላይ ተጥሎአል። ወንዶች በወንዶች፣ ሴቶች በሴቶች ጋር ነውር ማድረግ እንደ ቀላል በሚቆጠርበት በዚህ ዘመን፣ ሰው ወንድ ይሁን ወይም ሴት እንኳን ለመለየት እጅብ ብዙዎች ግራ ተጋብተው ይገኛሉ። ገና ተጫውተው ያልጨረሱ ህጻናት ትልልቅ ነን በሚሉ ሰዎች እየተደፈሩ ህይዋተቸው የምድር ሲኦል እየሆነ ነው። እንደ ኖህ ዘመን እውቀትና ስልጣኔ በዝቶአል በሚባልበት ዘመን የመንፈሳዊና ሞራላዊ ውድቀት በሰው ልጅ ላይ የበዛው በአጋጣሚ ይሆን?!  ብዙ ምርምሮችና መረጃዎች ይህ በአጋጣሚ እንዳልሆነ ያስረዳሉ። ምናልባት እነዚያ በኖህ ዘመንና ከዚያም በኋላ በምድር ላይ ነበሩ የተባሉት ኔፊሊም ዛሬም እንደገና በስውር በምድር ላይ እየሰሩ ይሆን?!! በማርች 2017 የወጣው የመለከት ድምጽ መጽሔት ቁጥር 5 (አምስት) በዚህ ጉዳይ ላይ ሰፋ ያሉ ሃሳቦችንና መረጃዎችን ይሰጣል። መጽሔቱን ከሚከተለው የመለከት ድምጽ ብሎግ አድራሻ ላይ ማግኘት ይቻላል።  http://voice-of-trumpet-amharic.blogspot.ca ወንድማችሁ ዶ/ር በፈቃዱ አድማሱ።



ሰማያት እየተናገሩ ናቸው!! በፊታችን ሰኞ ኦገስት 21፣ ከ99 ዓመታት በኋላ አሜሪካን ከምእራብ እስከ ምስራቅ የሚያቋርጥ ሙሉ የጸሃይ ግርዶሽ ይሆናል። ይህ ምልክት ምናልባት በአሜሪካ ወይም በዓለም ሁሉ ላይ ሊመጣ ስላለ የትልቅ ጥፋት የቅድሚያ ማስጠንቀቂያ ይሆን ???

ሰማያት እየተናገሩ ናቸው!! በፊታችን ሰኞ ኦገስት 21፣ ከ99 ዓመታት በኋላ አሜሪካን ከምእራብ እስከ ምስራቅ የሚያቋርጥ ሙሉ የጸሃይ ግርዶሽ ይሆናል።  ይህ ምልክት ምናልባት በአሜሪካ ወይም በዓለም ሁሉ ላይ ሊመጣ ስላለ የትልቅ ጥፋት የቅድሚያ ማስጠንቀቂያ ይሆን ???

NASA ከሚባለው የአሜሪካ የህዋ ምርምር ድርጅት በድረ ገጹና በተለያዩ መገናኛ ብዙኃን እንዳስታወቀው፣ ሰኞ ነሐሴ 21 ቀን 2017 ዓም በሰሜን ምእራብ ከምትገኘው ከኦሪጎን ክፍለ ሃገር እስከ ቻርልስተን ደቡብ ካሮላይና ድረስ ጸሃይ በቀን እንደምትጨልም ተገልጿል። ጸሃይ ፈጽማ በምትጨልምበት መስመር ላይ ያሉ ብዙ ወረዳዎችና ከተማዎች ከ2 እስከ 3 ደቂቃዎች ለሚያህል ጊዜ ቀኑ ፈጽሞ እንደሚጨልምና ሌሎቹ የአሜሪካ ክፍሎችም ደግሞ ከዚያ ላጠረ ሰዓትም ቢሆን ግርዶሹን እንደሚያዩ ይኸው የNASA መረጃ ያመለክታል።
የጸሃይና የጨረቃን ግርዶሽ እንዲሁም ሌሎችን በሰማይ ከዋክብትና ፕላኔቶች አልፎ አልፎ የሚታዩ ምልክቶችን፣ በሰው ዘርና በዓለም መንግስታት ታሪክ የታዩ ትልልቅ ክስተቶችን እና መጽሐፍ ቅዱስ ስለነዚህ ክስተቶች የሚናገረውን በቅርብ የሚያጠኑ ምሁራን፣ ተመራማሪዎችና ታሪክ ጸሃፊዎች በፊታችን ሰኞ እንደሚታየው አይነት የጸሃይ ግርዶሽ ዓይነት በዚሁ በኦገስት 21 ቀን 1914 ዓም በምስራቅ አውሮፓ ታይቶ እንደነበር ያስታውሱና፣ ያ ግርዶሽም በአውሮፓ በጥቂት አገሮች ጠብ ተጀምሮ የነበረው ጦርነት የአንደኛውን የዓለም ጦርነት መነሳት ያመለከተ እንደነበር ያስረዳሉ። በጥቂት አገሮች መካከል በተነሳ ጠብ ከ2 ወር በፊት ተነስቶ የነበረው ግጭት ብዙ ሚሊዮን ህዝቦችን ወደ ጨረሰና ታላላቅ የዓለም መንግስታትና ግዛቶችን ወዳፈራረሰው የዓለም ጦርነት መለወጡ በታሪክ የተዘገበ ነው። የአሜሪካን ግዛት ሁሉ የሚያቋርጥ ሙሉ የጸሃይ ግርዶሽ ለመጨረሻ ጊዜ ታይቶ የነበረው በ June 8, 1918 ነበር። ጊዜው አንደኛው የዓለም ጦርነት እያበቃ የነበረበት ቢሆንም፣ ከዚያው በመቀጠል ግን በአሜሪካ ብቻ ስድስት መቶ ሰባ አምስት ሺ ሰዎችን የገደለና በዓለም በሙሉ ደግሞ ከ ሃምሳ እስከ አንድ መቶ ሚሊዮን የሚቆጠሩ ህዝቦችን የፈጀ የወረርሽኝ በሽታ ተከስቶ እንደነበር ታሪክ ይዘግባል። ባለፉት ጥቂት ወራት በአሜሪካና በሰሜን ኮሪያ መካከል ያለውን ከፍተኛ ውጥረትና የኑክሊየር ጦርነት አደጋ የሚከታተሉ ደግሞ ይህ ሰኞ ኦገስት 21 በአሜሪካ ላይ የሚከሰተው ግርዶሽ የመጀመሪያው የኮሪያ ጦርነት ከመጀመሩ በፊት በ May 9, 1948 በሰሜንና በደቡብ ኮሪያ መካከል አቋርጦ የሄደውን የጸሃይ ግርዶሽ ያስታውሳሉ።
መጽሐፍ ቅዱስ እግዚአብሔር ጸሐይን ጨረቃና ከዋክብትን የፈጠራቸው ብርሃንን እንዲሰጡ፣ ለቀንና ለወቅቶች፣ ለወራትና ለዓመታት መቁጠሪያ እንዲያገለግሉ ብቻ ሳይሆን ለምልክት መስጫም እንደሆነ ኦሪት ዘፍጥረት ምእራፍ 1 ቁጥር 14 እስከ 19 ያስረዳል። አዳም ለእንስሳት ሁሉ ስምን እንደ ሰጠ የሰማይ ብርሃናትን ሁሉ ስም የሰጣቸውና ስራቸውንም የመደበላቸው እግዚአብሔር ራሱ ነው። መዝሙር 147፡4 ኢዮብ 38፡31-33 ሌሎች ብዙ የመጽሐፍ ክፍሎችም እግዚአብሔር በየዘመናቱ እነዚህን የሰማይ ብርሃናትን በመጠቀም ለሰው ልጆች መልእክቶችን፣ ምልክቶችንና ማስጠንቀቂያዎችን እንደ ሰጠ ይመሰክራሉ። ለምሳሌ ያህል ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተወለደ ጊዜ የምስራቅ ጠቢባን (ሰብአ ሰገል) ያወቁት በሰማያት ላይ የተገለጠውን ምልክት በመረዳታቸው ነው። በመስቀል ላይ በሞተ ጊዜ ጸሃይ እንደ ጨለመች ሉቃስ 23፡44-49 ማርቆስ 15፡33 እና ማቴዎስ 27፡45 ይመሰክራሉ። ከዚያ ቀደም ሲልም ነቢዩ ዮናስ ለነነዌ የንስሃን መልእክት ከመስበኩ ቀደም ብሎ በነነዌ ከተማ ላይ ያለፈ የጸሃይ ግርዶሽ ተከስቶ እንደነበር በNASA ድረ ገጽ የተደገፈ መረጃን ከብዙ ምንጮች ማየት ይቻላል። የ ቡር ሳጋል ግርዶሽ (Bur Sagale) ተብሎ የሚጠራው ያ የጸሃይ ግርዶሽ በ June 15, 763 ዓመተ ዓለም ተከስቶ እንደነበር የጥንት ታሪክ መረጃዎችና NASA ያከማቻቸው ያለፉት አምስት ሺ አመታት የጸሃይና ጨረቃ ግርዶሽ መረጃ ያሳያሉ። ሌሎች ታላላቅ ጥፋቶች በምድር ላይ ከመከሰታቸው ቀድሞ በጸሃይና በጨረቃ ግርዶሽ እንዲሁም በከዋክብት በሚሰጡ ምልክቶች እግዚአብሔር ለሰው ልጆች አስቀድሞ የንስሃ ጥሪና ማስጠንቀቂያ መስጠቱንም መጽሐፍ ቅዱስ ይመሰክራል። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ዳግም ምጽዓቱ መቃረቡን ከሚያሳዩት ነገሮች አንዱ በጸሃይ፣ በጨረቃና በከዋክብትም የሚታዩ ታላላቅ ምልክቶች እንደሚሆኑ ተናግሮአል። ሉቃስ 21፡25-28
በአሜሪካ ላይ የሚከሰተው የዘንድሮው (ኦገስት 21 ሰኞ) የጸሃይ ግርዶሽ የብዙ የመጽሐፍ ቅዱስ አዋቂዎችን ሃሳብ የሳበውና ያስፈራው ደግሞ ግርዶሹ የሚከሰተው አይሁድ በየዓመቱ ለ 40 ቀን የንስሃ ጊዜን ከሚጀምሩበት የኤሉል ወር መጀመሪያ አንድ ቀን ቀድሞ መሆኑ ነው። ከብሉይ ኪዳንና ከእስራኤል ታሪክ እንደምንረዳው ሰኞ ኦገስት 21 በአይሁድ (የጥንቱ የመጽሐፍ ቅዱስ ቀን አቆጣጠር) ኦቭ 30 ነው። ከማክሰኞ ኤሉል 1 ጀምሮ እስከ ማስተሰረያ ቀን (ቲሽሪ 10) ድረስ አይሁድ ሁሉ ንስሃ የሚገቡበት ቀን ነው። ይህ አርባ ቀን ሲያልቅም በሰማያት ላይ ሌላ አስገራሚ ምልክት እንደሚታይ NASA ገልጾአል። ስለዚያ ምልክት ደግሞ በሚቀጥለው መልእክቴ እገልጻለሁ። እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ከጥንት ጀምሮ በብዙ መንገድ በቀጥታ በተገለጸ ቃሉ፣ በህሊና፣ በተፈጥሮ ስራዎቹ፣ በሰማይ ብርሃናት በሚገለጹ ምልክቶች፣ በመላእክት፣ በነቢያት፣ በህልምና በራእይ ከገለጸ በኋላ በዘመኑ መጨረሻ ደግሞ ራሱ ልዑል አምላክ የሰውን ሥጋ ለብሶ በመምጣት በክርስቶስ ተናግሮአል። ዛሬም እየተናገረ ነው። እኛ የመስማትንና የመረዳትን ጸጋ እንለምን እንጂ እግዚአብሔር ከመናገር ዝም ብሎ አያውቅም።
በዓለም ላይ ታላቁ ኤኮኖሚና የጦር ኃይል ያላት አሜሪካ ባለፈው ዓመት በተደረገ ምርጫ ያልተጠበቁት ሰው በፕሬዝደንትነት መመረጣቸውን ተከትሎ በአገሪቱ ውስጥ የሚታየውን የፖለቲካ መመሰቃቀል፣ እንደ ሩሲያ፣ ቻይና፣ ኢራንና ሰሜን ኮሪያ ጋር ካሉ አገሮች ጋር አገሪቱ የገባችባቸውን ውጥረቶች እንዲሁም በምድሪቱ የሚታየው ማህበረሰባዊ ውጥረቶች፣ መንፈሳዊና የሞራል ውድቀት የሚያሳዝናቸው የአገሪቱ ክርስቲያኖች እግዚአብሔር ለምድራቸው ምህረትን እንዲያደርግ የንስሃና የጸሎት ጥሪዎችን ካወጁ ውለው አድረዋል። እነዚህን ሁኔታዎችና በሰማያትም ላይ የሚከሰቱትን የዘንድሮውን የጸሃይ ግርዶሽና በሴፕቴምበር 23 የሚከሰተውን ታላቅ የሰማያት ምልክት ከግምት ውስጥ በማስገባት ነው ብዙ የአሜሪካ ክርስቲያን መሪዎች አገሪቱ በንስሃ እግዚአብሔርን እንድትፈልግ ጥሪ እያደረጉ ያሉት።  በዚህች በምድር ላይ ባለች ኃያል አገር ላይ የሚፈጠር ቀውስ በአንድም በሌላም መንገድ የማይነካው አገርና ህዝብ በምድር ላይ የለም ማለት ማጋነን አይሆንም። ስለዚህ ሁላችንም ለዚህች አገር ሰላምና ምሕረት እንጸልይ። ከዚህ ጋር ተያይዞ ያለው ሪፖርት ስለ ኦገስት 21 የጸሃይ ግርዶሽና ከላይ ልገልጻቸው ስለጀመርሁት ሃሳቦች የበለጠ መረጃን ይሰጣል።

እግዚአብሔር ይጠብቃችሁና ይባርካችሁ። ወንድማችሁ ዶ/ር በፈቃዱ አድማሱ።

የቀድሞው የናይጄሪያ ፕሬዝደንት ሰዎች ሁሉ ለጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ዳግም ምጽዓት እንዲዘጋጁ አሳሰቡ።

የቀድሞው የናይጄሪያ ፕሬዝደንት ሰዎች ሁሉ ለጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ዳግም ምጽዓት እንዲዘጋጁ አሳሰቡ።
የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ የምስራቹ ወንጌል ከመንግሥታት ቁንጮዎች እስከ ተራው ሰው ድረስ በአንድም በሌላም መንገድ እየደረሰ ነው። በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ አምነው የዘለዓለም ሕይወትን ገና ያላገኙትን ሁሉ በፍቅር ወንጌሉ ለመጋበዝና፣ በእርሱ ያመኑት ሁሉ ደግሞ የዳግም ምጽዓቱ ተስፋ መቃረቡን በማወቅና በማመን እንዲበረታቱ እግዚአብሔር ትንንሾችንም ትልልቆችንም ሰዎች እየተጠቀመ ነው። በአገራቸው በናይጄሪያ የፕሬዝደንትነት አገልግሎት ጊዜአቸውን ሲጨርሱ የመንግስትን ሥልጣንን በሰላም ለሚቀጥለው መሪ በማስረከባቸው እንደ መልካም መሪ ምሳሌ ከሚጠቀሱት የአፍሪካ መሪዎች አንዱ የሆኑት የቀድሞው ጀነራል ኦሉሴጉን ኦባሳንጆ የምድር ነገስታት ሁሉ ንጉስ፣ የጌቶቹም ሁሉ ጌታ የሆነው የጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ዳግም ምጽዓት መድረሱን መናገራቸው ብዙ ሰባኪዎች አስተማሪዎች የሚናገሩት ቢሆንም፣ በህዝቧ ብዛት በአፍሪካ አንደኛ የሆነችው የዚህ አገር ፕሬዝደንት የነበሩት እኒህ ሰው ይህን እውነት በአደባባይ መናገራቸው ለብዙ ሰዎች ምስክርነት ነው።

እስከ ጥቂት አሰርት ዓመታት ድረስ የክርስትና እምነት ዋና ምሰሶዎች ነን ሲሉ የነበሩት የምእራቡ ዓለም አብያተ ክርስቲያንና መንግስታት የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት ጥለውና ወንጌልን ረስተው ወደ ባዕድ አምልኮ እየገቡ ባለበትና ሰለጠነ የሚባለው ዓለም ብዙ ህዝብ ፈሪሃ እግዚአብሔርንና ሰብዓዊ ህሊናን ጥሎ ለሰዶምና ለገሞራ እንኳን ያልበጀ የዓመጽ የኑሮ ዘይቤን እንደ ጌጥ እያንጠለጠለ ያዙኝ ልቀቁኝ በሚልበት በዚህ ዘመን፣ እግዚአብሔር ድሃና ያልተማረ ተብሎ በባለጸጋው ዓለም ወደታች ይታይ ከነበረው ከአፍሪካ የወንጌልን እውነት ለዓለም ሁሉ ሲልክ ማየቱ እጅግ አስደናቂ የፈጣሪ ስራ ነው። በእርግጥም ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ዳግም ተመልሶ ይመጣል። ቀኑንና ሰዓቱን አናውቅም፣ ለማንኛውም ግን ማንም ሰው በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ካልሆነ በቀር ወደ እግዚአብሔር መድረስ አይችልምና ንስሃ ገብቶ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን የመቀበያው ሰዓት ዛሬ ነው። ወንድማችሁ ዶ/ር በፈቃዱ አድማሱ።

የመለከት ድምጽ መጽሔት ቁጥር 9 ዛሬ ወጥቶአል


ምላስ መብልን እንደሚቀምስ ጆሮ ቃልን የሚለይ አይደለምን? ኢዮብ 12፡11

ላለፉት 18 ወራት ከምእራቡ ዓለም፣ በተለይም ከአሜሪካ፣ የሚመነጩትን ዜናዎች የሚያዳምጥ ሰው “የውሸት ዜና” ወይም “Fake News” የሚለውን ስም ሳይሰማ አይቀርም። እነዚህ “የውሸት ዜናዎች” የሚፈጠሩትና የሚሰራጩት ደግሞ ታላላቅ በሚባሉትና ብዙ ቢሊዮን ዶላር ገቢና ወጭ ባላቸው እጅግ ብዙ ህዝብ በሚያዳምጣቸው እንደ CNN, ABC, CNBC እና MSNBC ያሉ የዜና አውታሮች ነው። “የውሸት ዜናዎች” ተብለው የሚሰራጩት ዜናዎች ደግሞ ዛሬ በስልጣን ላይ ያሉትን የአሜሪካውን መሪ በማይወዱ፣ እንዳይመረጡ ሲጥሩ በነበሩ፣ ዛሬም የሰውየውን በስልጣን ላይ መቀመጥ ስለሚጠሉ በሚቻላቸው መንገድ ሁሉ ከቦታቸው ለማውረድ ቆርጠው በተነሱ ከመገናኛ ብዙኃን በስተጀርባ ባሉ ታላላቅና ባለጸጋ ሰዎች ነው።
ይህን መረጃ እዚህ ጋ ያቀረብኩበት ምክንያት ስለ አሜሪካ የፖለቲካ ሁኔታ መረጃ ለመስጠት ሳይሆን “የውሸት ዜና” የሚባለውን ሃሳብ ስመለከት፣ ጽንሰ ሃሳቡ አዲስ እንዳልሆነና መጽሐፍ ቅዱስ ከብዙ ሺህ ዓመታት ጀምሮ በእግዚአብሔር ስም ስለሚሰራጩ የሃሰት ትንቢቶች፣ ትምህርቶችና ምክር መስለው ስለሚሰራጩ ክፉና አጥፊ የሃሰት መረጃዎች መናገሩን ሳስተውል ነው። በኤድን ገነት ለሔዋን በእባቡ የቀረበላት ድንቅ የሚመስል ዜና የውሸት ዜና ነበር። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ታዲያ እግዚአብሔር ለሰው ልጆች በነቢያቱ፣ በሐዋርያትና በሌሎችም ቅዱሳን ሰዎች ከሚገልጸው እውነት ጋር የሚመሳሰሉ ሃሳቦችን፣ትንቢቶችን እና ትምህርቶችን  ጠላት ዲያብሎስ በየጊዜው በሰዎች መካከል ያሰራጫል። በብሉይ ኪዳን ዘመን የሃሰት ነቢያት ነበሩ። በአዲስ ኪዳን ደግሞ እንዲሁ ከሃዋርያት ዘመን ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ብዙ የሃሰት አስተማሪዎችና የስህተት ትምህርቶች እንደተሰራጩ መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል። እግዚአብሔር ዘመናትን በሙሉ በቅድሚያ ስለሚያውቅ፣ ያለፉትንና ያሉትን የሃሰት ትምህርቶች ብቻ ሳይሆን ወደፊትም የሚከሰቱትን አስቀድሞ አይቶ በኢየሱስ ክርስቶስ የሚያምኑ ህዝቡ ከነዚያ ትምህርቶች እንዲጠነቀቁ እውነቱን በብሉይና በሃዲስ ኪዳን መጻህፍት አስቀምጦልናል።

ክርስቲያኖች ሁሉ መንፈሳዊ የሚመስሉ የሃሰት ትምህርቶችን ከእውነቱ መለየት የምንችለው በመጀመሪያ እውነቱን ሁሉ የሚያስተምረንን መጽሐፍ ቅዱስን በሚገባ ስናውቅ ነው። እውነቱን ጠንቅቀን ካላወቅንና እምነታችን በአለቱ በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ መመስረቱን ካላረጋገጥን በየጊዜው በሚነሱ የሃሰት ትምህርቶችና ፍልስፍናዎች መወሰዳችን የግድ ነው። የስንዴን ዘር ወይም ተክል አይቶ የማያውቅ ሰው ስንዴውን ከእንክርዳዱ ሊለይ አይችልም። የእውነት መለኪያው ደግሞ በመጽሐፍ ቅዱስ የተገለጸው የእግዚአብሔር ቃል እንጂ አንድን ትምህርት ወይም አስተማሪ የሚከተሉት ሰዎች ብዛትና የሃሳቡ ዘመናዊ ወይም መንፈሳዊ መምሰል አይደለም። እውነት፣ መንገድና ህይወት ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ስንዴውን ከእንክርዳዱ እንዴት ልንለይ እንደምንችል፣ በተለይም ደግሞ በዚህ ዘመን በሰፊው እየተናፈሰ ያለውን “የብልጽግና ወንጌል” የሚባለውን ትምህርት ከእውነተኛው ወንጌል መለየት እንድንችል የሚረዱንን አንዳንድ ሃሳቦችን የያዘችው የመለከት ድምጽ መጽሔት ቁጥር 9 ዛሬ ወጥታለች። ባለፉት ብዙ ወራት ጥቂት ሲቀርብ የቆየው የዶ/ር ዘመድኩን ተሻለ የህይወት ምስክርነት ክፍል ስድስትም በዚሁ እትም ቀርቦአል። የመጽሔቱን PDF ቅጂ በነጻ በመቅዳት (ዳውንሎድ በማድረግ) እንድታነቡና ለሌሎችም እንድታካፍሉ በትህትና እጋብዛችኋለሁ። ወንድማችሁ ዶ/ር በፈቃዱ አድማሱ።


ዓለም በብዙ አቅጣጫዎች 3ኛውን የዓለም ጦርነት ሊያስነሳ በሚችል ፍጥጫ ውስጥ ገብታለች

ዓለም በብዙ አቅጣጫዎች 3ኛውን የዓለም ጦርነት ሊያስነሳ በሚችል ፍጥጫ ውስጥ ገብታለች
http://endtimeheadlines.org/2017/07/rumors-war-u-s-inches-war-north-korea-millions-die/

ባለፉት ወራት ደጋግሜ እንደጻፍሁትና ከታች ከተያያዘው ሪፖርት እንደምትረዱት፣ ልንረዳው በማንችለው ፍጥነት ዓለማችን ከዚህ በፊት ታይቶ የማይታወቅ ፍጅትን ሊፈጥር ወደሚችል ወደ ከፍተኛ ጦርነት እየተፋጠነች ነው። ብዙ ለመረጃዎች ቅርበት ያላቸው ባለሙያዎች ይህ ጦርነት የ3ኛው የዓለም ጦርነትና የኑክሊየር መሳሪያዎችም ስራ ላይ የሚውሉበት ሊሆን ይችላል እያሉ ያስጠነቅቃሉ። ከሁለተኛው የዓለም ጦርነትና ከቀዝቃዛው ጦርነት በኋላ ታይቶ የማይታወቅ የኤኮኖሚ እቀባን አሜሪካ በሩሲያ ላይ ጥላለች። የአሜሪካው ምክር ቤት የገዛ የራሳቸው የአሜሪካው ፕሬዝደንት እንኳን እቀባውን እንዳስፈላጊነቱ በማስተካከል ከሩሲያ ጋር በንግግር በሚደረግ መግባባት እንዳይደርሱ እጅ እግራቸውን የሚያስር እቀባን ያሳለፉት 419 ለ3 እና 98 ለ 2 በሆነ ድምጽ ነው። ፕሬዝዳንቱም የምክር ቤቱን ውሳኔ ህግ እንዲሆን የፈረሙት ምንም ምርጫ ስለሌላቸው እንጂ እንደማይስባሙበት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትራቸው በአደባባይ ተናግረዋል። ታሪክን የሚያስታውስ ካለ፣ ጃፓን የአሜሪካ ግዛት የሆነውን ፐርል ሃርበርን በቦምብ የደበደበችው አላላውስ የሚል የኤኮኖሚ እቀባ በአሜሪካ ስለተደረገባት ነበርና፣ የአሁኑ የአሜሪካ ግፊትም ሩሲያ ሳትወድ ተገፍታ ወደ ጦርነት እንድትገባ ለማድረግ ነው የሚሉት የራሷ የአሜሪካ የቀድሞ ጀነራሎችና ታሪክ ታዛቢዎች ናቸው። ሩሲያም ይህን ለመበቀል ከ750 በላይ የሆኑ የአሜሪካ ዲፕሎማቶችን ከአገሯ አባርራለች፣ ዲፕሎማቶቹ ይጠቀሙባቸው የነበሩ የመዝናኛ እና የእቃ ማከማቻ ቤቶችንም ነጥቃለች።  ፍጻሜ  ታላላቆቹ የምድር መንግስታት ሰራዊት በብዙ የዓለም ክልሎች ግንባር ለግንባር ተፋጥጠው ለጦርነት ከፍተኛ ዝግጅቶችን እያደረጉ ነው። ባለፉት ሁለት ሳምንታት ብቻ አሜሪካ አዲስና እስካሁን ካሏት ሁሉ ትልቅ የጦር አውሮፕላን ተሸካሚ መርከብን ሰርታ አሰማርታለች። ከ 3 ቀናት በፊት ቻይና የጦር ሰራዊቷ የተመሰረተበትን 90ኛ ዓመት በምታከብርበት ጊዜ እስከ ዛሬ ወደ አደባባይ ወጥተው ያልታዩ አስፈሪ የጦር መሳሪያዎችን አሳይታለች። ሩሲያም ዓመታዊ የባህር ኃይሏ በሚከበርበት ቀን ከ 100 በላይ የጦር መርከቦችን በማሰለፍ ኃይሏን አሳይታለች። የቀድሞ የሶቪየት ህብረት አካል በነበሩት በቦልቲክ ሪፑብሊኮችና በጆርጂያ አሜሪካና አጋሮቿ የጦር ልምምድ ሲያደርጉ ከርመዋል። በፋርሱ ባህረ ሰላጤ የአሜሪካና የኢራን የባህር ኃይሎች ከመገላመጥ አልፈው በአንድ ሳምንት ጊዜ ያህል ብቻ የአሜሪካ ጦር የኢራንን ጀልባዎች ለማስፈራራትና ለማስጠንቀቅ እንደተኮሱ ተዘግቦአል። ልብ ብሎ ለሚያዳምጠው የሚያስፈራ የጦርነት ነጋሪት በምድር እየተደለቀ ነው። ይህ እየተፈራ ያለው ጦርነት በእርግጥ ከተነሳ 3ኛው የዓለም ጦርነት እንደሚሆንና በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች እንደሚያልቁ ብዙ አዋቂዎች ያስጠነቅቃሉ። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዳግም የመምጫው ዘመን ሲቃረብ በምድር ላይ ጦርነትና የጦርነት ወሬ እጅግ እንደሚበዛ ተናግሮአል። ታዲያ ምን እናድርግ? ሊሆን ያለው ሁሉ ይሆናል። በተቻለን መጠን መረጃዎችን ማግኘታችንና በግላችንና ለቤተሰባችን እንዲሁም ለህብረተሰባችን ልናደርገው የምንችለው ዝግጅት ካለ በጊዜው ማድረጉ መልካም ነው። በክርስቶስ የምናምን ክርስቲያኖች ሁሉ ለሰላም እንጸልይ። ጌታን ኢየሱስ ክርስቶስን እንደ አዳኛችን ያልተቀበልን ሁሉ ደግሞ ከሁሉ በላይ የነፍሳችንን የዘለዓለም ኢንሹራንስ ማግኘቱ አንገብጋቢ ነው። ያ ኢንሹራንስ ደግሞ በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን ብቻ የሚገኘው የዘለዓለም ሕይወት ተስፋ ነው። ለደህንነታችን የሚከፈለውን ሁሉ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ከፍሎልናል። ዛሬም ኑ እያለ የሰውን ልጆች ሁሉ ወደ ደህንነት ይጋብዛል። ጥሪውን ሳንመልስና ዛሬ ነገ ስንል ጊዜ አይለፍብን። ማንም አያታልለን። ይህችን ህይወት ጨርሰን ከዚህ ዓለም ከሄድን በኋላ ሌላ የመዳኛ መንገድ የለም። የእግዚአብሔር ሰላም ይብዛላችሁ። ወንድማችሁ ዶ/ር በፈቃዱ አድማሱ። 

ሰው ሰራሽ ቴክኖሎጂ የምድርን አየር እያናጋ ነው፣ የምድር መንቀጥቀጥና እሳተ ገሞራም የማፈንዳት ጥፋቶች ይሰራሉ

በኖኅ ዘመን እንደነበረው የሰው ልጅ እግዚአብሔርን ክዶ ራሱ አምላክ ለመሆን ሲቃጣው በራሱ እና በእግዚአብሔር ፍጥረት ላይ ትልቅ ጥፋትን እየፈጠረ ነው። ዶ/ር በፈቃዱ አድማሱ ጌታ አምላክ የሰው ልጅ ሊ...