ሰው ሰራሽ አእምሮ የሰውን ልጅ መተካትና የሰውንም ዘር ማጥፋት የሚችልበት ዘመን
ላይ ደርሰናል ተባለ
ከኦሪት ዘፍጥረት እስከ ዮሐንስ ራእይ ድረስ የተጻፈውን የእግዚአብሔርን ቃል፣ በተለይም
ደግሞ ስለመጨረሻው ዘመን፣ ስለ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ዳግም ምጽዓት፣ በዘመኑ መጨረሻ ላይ ስለሚገለጸው የእግዚአብሔር መንግስት
እና ስለዘለዓለም ፍርድ የተጻፉትን ትንቢቶች ከየእለቱ ዜናዎች ጋር በማነጻጸር ብናደምጣቸው እግዚአብሔር በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ
በኩል ከፍጥረት መካከል የዋጃቸውን ሕዝቡን ወደራሱ የሚሰበስብበትና በዓመጸኛው ዓለም ላይ የሚፈርድበት ዘመን እጅግ እየተቃረበ መሆኑን
እናስተውላለን። ስለዚህ ዘመን መጨረሻ ከተጻፉት ትንቢቶች አንዱ እንዲህ ይላል፤
ሰባቱ ነጎድጓድ በተናገሩ ጊዜ ልጽፍ አሰብሁ፣ ከሰማይም
ሰባቱ ነጎድጓድ የተናገሩትን በማኅተም ዝጋው፣ አትጻፈውም የሚል ድምጽ ሰማሁ። …….. ዳሩ ግን ሰባተኛው መልአክ ሊነፋ ባለው ጊዜ ድምጹም በሚሰማበት ዘመን ለባሪያዎቹ ለነቢያት የምስራች እንደሰበከላቸው
የእግዚአብሔር ምስርጢር ይፈጸማል አለ። ራዕይ 10 ቁጥር 4 እና 7
ባለፉት ጥቂት ቀናት በቤጅንግ ቻይና እየተካሄደ ባለው የዓለም አቀፉ ተንቀሳቃሽ ኢንተርኔት ኮንፈረንስ (GMIC) ላይ
ንግግር ያደረጉት እውቁ የፊዚክስና የህዋ ምርምር ሊቅ ፕሮፌሰር ስቲቨን ሆውኪንግ እንዳሉት፣ የሰው ልጅ ራሱ የፈጠረው ሰው ሰራሽ
አዕምሮ (ARTIFICIAL INTELLIGENCE ወይም ባጭሩ AI) ከራሱ ከሰው ልጅ ችሎታ እኩል ወይም በላይ የሆኑ ነገሮችን ሊሰራ የሚችልበት ደረጃ ደርሷል፣
በብዙ መስመሮችም ላይ ይህ ሰው ሰራሹ አእምሮ ከሰው ልጅ ከራሱም ችሎታ በላይ የላቁ ነገሮችን ስለሚሰራ በከፍተኛ ፍጥነት የሰውን
ልጅ ህልውናና በዚህ ምድር ላይ የመኖር አስፈላጊነት ከጥያቄ ውስጥ እያስገባው ነው ብለዋል። በመጨመርም፣ ይህ ቴክኖሎጂ የሰውን
ልጅ ለመርዳትና ችግሮቹን ለመርዳት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ሊያደርግ የሚችል ቢሆንም፣ እንደፈለገው እንዲሆን ከተለቀቀ ግን የሰውን ዘር
ፈጽሞ ሊጎዳና ሊያጠፋም እንደሚችል አስጠንቅቀዋል። “ቆም ብለን ማሰብ ያለብን አሁን ነው” ያሉት እኒህ ታዋቂ ምሁር፣ ይህ ቴክኖሎጂ
በሰው ልጅ ደህንነትና ህልውና ላይ ሊያመጣ የሚችለው ጥፋት በጣም እንደሚያሰጋቸው ከመናገር ወደ ኋላ አላሉም። የርሳቸውንም ሆነ
የሌሎች አዋቂዎችን ምክር የሚሰማ ወይም የሚያስተውል ይኖር ይሆን ?!!
የኮምፒውተርና የኢንተርኔት ቴክኖሎጂ እጅግ በመስፋፋት ዓለምን በሙሉ መሸፈን ከመጀመረባቸው
እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር ከ1990ዎቹ ጀምሮ እነዚህ ሰው ሰራሽ ቁሾች (HARDWARE) የመረጃ መረቦችና (NETWORKS) እና በሰው የተጻፉ የኮምፒውተር ትእዛዞች
(SOFTWAREስ) ቅንብሮች
እጅግ ከፍተኛ ወደሆነ ልእቀት በመድረስ ዛሬ የኮምፒውተር ቴክኖሎጂ ቀደም ሲል የሰው ልጅ ብቻ ይሰራቸዋል የሚባሉ ነገሮችን በሙሉ
ሊያከናውን ወደሚችልበት ደረጃ ደርሷል። በAI የሚመሩ ቁሶችና ሶፍትዌሮች ቤት ያጸዳሉ፣ መኪና ይነዳሉ፣ አውሮፕላን ያበራሉ፣ በፋብሪካዎች
ውስጥ እቃዎችን ይሰራሉ፣ ይገጣጥማሉ፣ ትልልቅ ፋብሪካዎችን፣ የኃይል ማመንጫዎችን፣ የውሃና የፍሳሽ አገልግሎት መሳሪያዎችን ይቆጣጠራሉ፣
በራዳርና ሌሎች የተለያዩ መሳሪያዎች ድምጾችን በመስማት፣ ምስሎችን በማየት፣ ሽታዎችንና ጣእሞችን በመለየት መረጃን ይሰበስባሉ፣
ከተራ የጦር መሳሪያዎች እስከ ኑክሊየር ሚሳኤሎች ድረስ የመቆጣጠርና ሲፈቀድላቸውም ኢላማ የመለየትና የመተኮስ እንዲሁም ከጠላት
የተተኮሱ መሳሪያዎችን የመለየትና የመምታት ችሎታ አላቸው። በሆስፒታል ቀዶ ጥገና የማድረግ፣ ወደ ህዋ የሚመጥቁ መንኮራኩሮችን የመምራት፣
የኢኮኖሚ፣ የፋይናንስና የኢንሹራንስ እንዲሁም የላቁ የምህንድስናና ሳይንሳዊ ቀመሮችንና ስሌቶችን የማከናወን፣ የምርት ጥራትን የመቆጣጠርና
ሌሎችም የላቁ ስራዎችን የመስራት ችሎታ አላቸው።
ሰው ሰራሹ አእምሮ (AI)
ዛሬ የሚቆጣጠረው
ኮምፒውተሮችን፣ ታብሌቶችን፣ የእጅ ስልኮችን እና በየእለቱ በግላችንና በድርጅት ወይም በጋራ የምንጠቀምባቸውን ቁሶች ብቻ አይደለም።
እንደ GOOGLE, FACEBOOK, TWITTER, INSTAGRAM
ያሉ እና ሌሎችም
በሰፊው የምንጠቀምባቸው ሶፍትዌሮች ስራቸው ለእኛ መረጃ መስጠትና የምንፈልገውን ነገር ማፈላለግ ብቻ አይደለም። እያንዳንዳችን በተደጋጋሚ
የምንፈልጋቸውን ነገሮች ያጠናሉ፣ ከማን ጋር ምን እንደምንነጋገር ወይም እንደምንጻጻፍ፣ መቼ ወጥተን መቼ እንደምንገባ፣ ምን እንደምንችል፣
ምን እንደምንገዛና እንደምንሸጥ፣ ምን እንደምናምን፣ ምን እንደምንደግፍና እንደምንቃወም፣ ምን እንደምንጠላላን እንደምንወድ ሳይቀር
መረጃን በመሰብሰብ እኛንና ባህርያችንን ያጠናሉ፣ አንድን ቋንቋ ወደ ሌላ ይተረጉማሉ፣ የሰውን ንግግር በማዳመጥና መልስ በመስጠት
ድሮ ብዙ ሰዎች ይሰሩአቸው የነበሩ ስራዎችን በቀላሉ ያከናውናሉ። ከነዚህ ሰው ሰራሽ አእምሮዎች በስተጀርባ ያሉ ባለቤቶች ከፈለጉም
እንቅስቃሴያችንና ግንኙነቶቻችንን በሙሉ እነሱ ወደሚፈልጉት አቅጣጫ የመግራትና ሲያስፈልግም እንቅስቃሴያችንን ወይም ንግግራችንን
የመዝጋት ችሎታው አላቸው። ለምሳሌ፣ ባለፈው ዓመት በአሜሪካ በተደረገው ብሔራዊ ምርጫ ላይ የGOOGLE ና የFACEBOOK ሶፍትዌሮች የቀኝ ክንፍ ወይም CONSERVATIVE
ወገኖች በምርጫው
ላይ ወደፊት እየመሩ ሲገኙ የነሱን ዜናዎች ሰዎች በቀላሉ እንዳያገኙአቸውና እንዳይደግፉአቸው ወደታች በመግፋት ያፍኑአቸው እንደነበር
በተደጋጋሚ ተገልጾአል። ስለዚህ እነ FACEBOOK እና GOOGLE ወይም ሌሎቹ ነጻ መሳይ የብዙኃን መገናኛዎች እኛ እንደምንገምተው
ስራቸው በቅንነትና በነጻ ለህዝቦችና ለሰዎች ሁሉ አገልግሎት መስጠት ሳይሆን ምርጫችንን፣ ዝንባሌያችንን እና ፍላጎታችንንም ሳይቀር
ለመለወጥ ችሎታው ያላቸው መሳሪያዎች ናቸው።
በእጃችን ባሉ ዘመናዊ ስልኮች፣ በየቤታችን ባሉ ቴሌቪዥኖች እና በእጃችን ላይ በምናስራቸው
ሰዓቶች፣ በምግብ ማቀዝቀዣዎች፣ በመኪናዎቻችንና ሌሎችም ቁሶች ውስጥ የሚቀመጡት ሶፍትዌሮች ያለንበትን ቦታና፣ በማንኛውም ጊዜ ምን
እየሰራን እንዳለ ጭምር ስለሚያውቁ፣ ችሎታው ያላቸው ሰዎችና ድርጅቶች ይህንን መረጃ በመጠቀም ሊያጠቁንና ሊጎዱንም ይችላሉ። በመለከት
ድምጽ መጽሔት ቁጥር 6 (ስድስት) ላይ እንዳቀረብሁት በቀላሉ በGPS እና በሌሎችም አድራሻ ጠቋሚ መሳሪያዎች አማካይነት ያለንበት
ቦታ ድረስ መጥው ሊያጠቁን የሚችሉ ነፍሳት መሰል መሳሪያዎች ከተሰሩ ውለው አድረዋል። ብዙዎች የዘመኑን ወታደራዊ ኃይላት የሚያጠኑ
ባለሙያዎችም የሶስተኛው የዓለም ጦርነት የሰውን ዘር ህልውና እጅግ ያሰጋል የሚሉት ይህ ሰው ሰራሽ አእምሮ በራሱ እንዲሰራ ከተለቀቀ
ሊያመጣ የሚችለውን እልቂት ከግምት ውስጥ በማስገባት ነው። እንደ ሩሲያና አሜሪካ እንዲሁም ቻይና ያሉ ታላላቆቹ አገሮች ዛሬ ሰውን
በትክክል የሚለዩና ካስፈለገ መማረክ ወይም ተኩሰው መግደል የሚችሉ በራሳቸው የሚንቀሳቀሱ፣ የሚያዩ፣ የሚሰሙና ውሳኔ ማድረግ የሚችሉ
መሳሪያዎችን በሰፊው እያመረቱ ነው። ምናልባት ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ዳግም ከመምጣቱ በፊት በምድር ላይ ስለሚመጣው ታላቁ የመከራ
ዘመን ሲናገር “እነዚያ ቀኖችስ ባያጥሩ ስጋ የለበሰ ሁሉ ባልዳነ ነበር፣ ነገር ግን እነዚያ ቀኖች ስለተመረጡት ሰዎች ያጥራሉ።”
በማለት በማቴዎስ 24 ቁጥር 22 ላይ የተናገረው ስለዚህ ጉዳይ ይሆን ?!
አተኩሮ ለተመለከተው የሰው ሰራሽ አእምሮ (artificial intelligence ወይም AI) ችሎታና በሱም የሚንቀሳቀሱ የሰላምና የጦርነት መሳሪያዎች፣ ስለሚያስፈራው ስለእግዚአብሔር
ቀን በጻፈው በነቢዩ በኢዩኤል ትንቢት (ምእራፍ 2 ቁጥር 1 እስከ
11) ላይ የተገለጹትን ነገሮች የሚመስል ባህርይ አላቸው። የኢዩኤል
ትንቢት አንዱ ክፍል እንዲህ ይላል፤
“ከፊታቸው አህዛብ ይንቀጠቀጣሉ፣ የሰውም ፊት ሁሉ
ይጠቁራል። እንደ ኃያላን ይሮጣሉ፥ እንደ ሰልፈኞችም በቅጥሩ ላይ ይወጣሉ፣ እያንዳንዱም በመንገዱ ላይ ይራመዳል፣ ከእርምጃቸውም
አያፈገፍጉም፣ አንዱ ካንዱ ጋር አይጋፉም፣ እያንዳንዱም መንገዱን ይጠበጥባል፣ በሰልፉ መካከል ያልፋሉ፣ እነርሱም አይቆስሉም። በከተማም
ያኮበኩባሉ፣ በቅጥሩም ላይ ይሮጣሉ፣ ወደ ቤቶችም ይወጣሉ፣ እንደ ሌባም በመስኮቶች ይገባሉ።” ኢዩኤል 2፤6፥9
ሰው ሰራሹን አእምሮ በተመለከተ መረዳት የሚገባን መንፈሳዊ ነገርም አለ። የሰው ዘር
ጠላት የሆነው ዲያብሎስ፣ ተከታዮቹ የወደቁት መላእክትና አጋንንት ግዑዝ በሆኑ ሃውልቶችና ጣዖታት ውስጥ በመሆን የሰው ልጆች ለዘመናት
እንዲሰግዱላቸው ካደረጉ፣ በሰው ሰራሽ አእምሮ በሚመሩ ነገሮች ውስጥ በመሆን የሰውን ልጅ ከማታለልና ሰው በእጅ የተሰራውን እንዲያመልክ
ከማድረግ ወደ ኋላ አይሉም። ምናልባትም በዮሐንስ ራእይ ምእራፍ 13 ቁጥር ላይ የተጻፈው “የአውሬው ምስል” የዓለም ህዝብ ሁሉ
ሃሰተኛው ክርስቶስ ከሞት ተነሳ ብሎ እንዲያምን የሚከወን በሰው ሰራሽ አእምሮ የሚመራ ቅርጽ ወይም ሰው መሳይ አካል ሊሆን እንደሚችል
ብዙ የትንቢት ምሁራንና ቴክኖሎጂውን በቅርብ የሚያጠኑ አዋቂዎች ይገምታሉ?!
ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን የግል አዳኙ አድርጎ የተቀበለና ጌታን በመታዘዝ የሚመላለስ
ክርስቲያን ሁሉ ከላይ የተጠቀሰውንና ሌሎችንም መሰል ዜናዎች ሲሰማ የጌታ ቀን እንደተቃረበ በማወቅ ራሱን ማዘጋጀት እንጂ መፍራት
ወይም መታወክ አያስፈልገውም። የእግዚአብሔርን ፍቅርና በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ለሰው ልጆች ሁሉ የተደረገውን የወንጌል ግብዣ ገና
ያልተቀበለ ማንኛውም ሰው ደግሞ ኃጢዓተኝነቱን በመገንዘብና እግዚአብሔርም በክርስቶስ ሞትና ትንሳኤ ምክንያት ይቅር እንደሚለው በማመን
ኢየሱስ ክርስቶስን የመቀበያው ቀን ዛሬ ነው። መቼ እንደሚሆን ቀኑን እና ሰዓቱን ባናውቅም ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ዳግም ተመልሶ
የሚመጣበት ቀን እጅግ እየተቃረበ ነው። በዚያን ቀን ለንስሃ ቦታ የለም። ያ ቀን የፍርድና እግዚአብሔር ስንዴውን ከእንክርዳድ የሚለይበት
ቀን ነው። የንስሃ ቀን ዛሬ ነው። እግዚአብሔር እርሱን የምንፈራበትና በንስሃ በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ወደሱ የምንመለስበትን
ልብ ይስጠን።
ወንድማችሁ ዶ/ር በፈቃዱ አድማሱ።