እንደ ተወደዱ ልጆች እግዚአብሔርን የምትከተሉ ሁኑ ኤፌሶን 5፡1
ዶ/ር በፈቃዱ አድማሱ (አፕሪል 25፣ 2018)
“መወለድ
ቋንቋ ነው” የሚለውን አባባል ዛሬ ምን ያህል እንደምናውቀው ወይም እንደምንጠቀምበት አላውቅም። አንዳንዶቻችን ድሮ ብለን በምንጠራው
ዘመን ግን አባባሉ ጥልቅና ጠንካራ መልእክቶች ነበሩት። ለምሳሌ ያህል በዚያ በድሮው ዘመን አንድ ሰው ማንነቱን ለሌሎች ለመግለጽና
ለማሳየት፣ ተቀባይነትን፣ ወይም ክብርን ለማግኘት ከሚያቀርባቸው መረጃዎች መካከል አንዱና ዋነኛው “የእገሌና የእገሌ ልጅ ነኝ”
ማለት ነበር። ያ ሰው የጠቀሳቸውን እገሌና እገሌን የሚያውቁ፣ ነገር ግን በጠቃሹ ባህርይ ላይ ጥርጣሬ ወይም ጥያቄ ያላቸው ሰዎች
ታዲያ “መወለድ ቋንቋ ነው” በማለት ያ ሰው መልካም ስም ያለው ቤተሰብ ተወላጅ ቢሆንም የእርሱ ባህርይ ግን ከወላጆቹ ወይም ከቤተሰቦቹ ማንነት ጋር እኩል ቦታ ወይም
ክብር ሊሰጠው የሚችል አለመሆኑን ያመለክቱ ነበር። የማንነትና የመልካም ባህርይ መረጃ ከሚያስፈልጉባቸው ነገሮች አንዱ ጋብቻ ነበር።
በዚያን ዘመን አንድ ወጣት አንዲትን ኮረዳ ለማግባት ለማጨት ሽማግሌዎች ወደ ልጅቱ ቤተሰብ ከመላካቸው በፊት የእርሱ ቤተሰብ ልጅቷ
የማን ልጅ ናት ብለው ይጠይቃሉ፣ ያጠያይቃሉ። ጉምጉምታውን የሰሙ የልጅቷ ቤተሰብም እንዲሁ ሊያጭ የሚፈልገው ሰው የማን ልጅ ነው
ብለው በዘመድ አዝማድ፣ በቅርብ ባልንጀሮችና በዘመድ አዝማድ ያጠያይቃሉ። የጨዋ ቤተሰብ ልጅ ናት፣ የጥሩ ቤተሰብ ልጅ ነው የተባለ
እንደሆነ ወደ መተጫጨትና ወደ ጋብቻ ከሚያመራው መንገድ ላይ አንድ እንቅፋት ተነሳ ማለት ነው። ይህ ብቻ ግን በቂ አልነበረም።
የልጁና የልጅቷ ማንነት፣ በተለይም ደግሞ እንደ ታማኝነት፣ ታታሪነት፣ ትጉነትና ተግባቢነት ያሉ ባህርዮቻቸው፣ ሙያ እናና ኃላፊነትን
የመሸከም ችሎታም በሁለቱ ቤተሰቦችና በሽማግሌዎች እንዲሁም በዘመድ አዝማድና በቅርብ ባልንጀሮች ይመዘኑ ነበር። የዘላቂ ትዳርን
መሰረት ጠንካራ ከሚያደርጉት ነገሮች መካከል የሁለቱ ተጋቢዎች ማንነት ማእከላዊ ስፍራን የሚይዙ ናቸው። የተጋቢዎቹን ማንነት ከሚቀርጹት
ነገሮች መካከል ደግሞ የሁለቱ ተጋቢዎች ቤተሰቦች ማንነት አንዱና ዋነኛው እንደሆነ ይታመን ነበር። ሌላው የሰርግ ዝግጅትና ሂደት፣
ጥሎሹ፣ ድግሱ፣ ስጦታው፣ የደስታ መግለጫው ወዘተ የጋብቻውን መመስረት የሚያሳምሩና የሚደግፉ ቢሆኑም መሰረታዊ ናቸው ለማለት አይቻልም። የዚህ አጭር መልእክት ትኩረት የአማርኛ
አባባሎችን ለማስተዋወቅ ወይም የጥንቱን ባህላዊ የመተጫጨትና የጋብቻ ስርዓት ዘወር ብሎ ለማየትና ለመገምገም ሳይሆን በጌታ በኢየሱስ
ክርስቶስ ያመንን ክርስቲያኖች ሁሉ ለዘለዓለም ሕይወትና ከክርስቶስ ጋር በክብር ለመኖር መዋጀታችንን በተመለከተ ከላይ የተገለጸውን
አባባል ተመርኩዞ አንዳንድ መሰረታዊ ነገሮችን ለማመላከት ነው።
በመንፈሳዊ
ሕይወት እያደግን ስንሄድ የደስታችን ምንጭ ምን መሆኑን እንገነዘባለን። መሰረታዊ እውነቶችን በአግባቡ እየተረዳን ስንመጣ ሙሉ በሙሉ
ልንገልጸው የማንችለውን የዘለዓለም ሕይወት፣ ደስታና ሰላም የሰጠንን እግዚአብሔርን ደስ ለማሰኘት እንናፍቃለን። ከነዚህ መሰረታዊ
እውነቶች መካከል አንዱ በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን የዘለዓለም ሕይወትን ያገኙ ሁሉ የክርስቶስ አካል የሆነችው የቤተ ክርስቲያን
ብልቶች መሆናቸው ነው። አዲስ ኪዳን ስለዚህ ሲናገር፤ “እናንተም የክርስቶስ
አካል ናችሁ እያንዳንዳችሁም ብልቶች ናችሁ” ይላል (1ኛ ቆሮንቶስ ምዕራፍ 12:27) ቤተ ክርስቲያን ደግሞ ያለ ነውርና ያለ ነቀፋ ሆና እንድትገኝ ለክርስቶስ ታጭታለች። ሐዋርያው
ጳውሎስ ይህን እንደዚህ ይገልጸዋል፤ “በእግዚአብሔር ቅንዓት
እቀናላችኋለሁና፣ እንደ ንጽሕት ድንግል እናንተን ለክርስቶስ ላቀርብ ለአንድ ወንድ አጭቻችኋለሁና፣” 2ኛ ቆሮ 11፡2 ለኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን በላከው መልእክት ደግሞ፡ “በውኃ መታጠብና ከቃሉ ጋር አንጽቶ እንዲቀድሳት ስለ እርስዋ ራሱን አሳልፎ ሰጠ፣ እድፈት
ወይም የፊት መጨማደድ ወይም እንዲህ ያለ ነገር ሳይሆንባት፣ ቅድስትና ያለ ነውር ትሆን ዘንድ ክብርት የሆነችን ቤተ ክርስቲያን
ለራሱ እንዲያቀርብ ፈለገ።” ይላል
(ኤፌሶን 5፡27)።
ልዑል
እግዚአብሔር በክቡር ልጁ ደም የዋጃት የቤተ ክርስቲያን፣ የክርስቶስ አካል፣ ብልቶች ከሆንን እና ጌታ አምላክ ደግሞ ቤተ ክርስቲያን
ቅድስት፣ ንጽህት እና ነውር የሌለባት እንድትሆን ካዘዘ፤ እኛም እያንዳንዳችን በቃሉና በመንፈሱ በመታጠብ ልንቀደስና ለእርሱም ቅዱስ
ቤተ መቅደስ ለመሆን ልንሰራ ያስፈልጋል። እግዚአብሔር ሰው በሰራው መቅደስ አይኖርም። በብሉይ ኪዳንም ሆነ በሐዲስ ጌታ እግዚአብሔር
ማደሪያውን ሊያደርግ የፈለገው በህዝቡ መካከል ነው። በብሉይ ኪዳን የምናያቸው በምድረ በዳ የነበረው የመገናኛው ድንኳንም ሆነ በኢየሩሳሌም
የነበረው ቤተ መቅደስ አገልግሎት ጌታ አምላክንና ሕዝቡን የማገናኛ ስፍራ መሆን ብቻ ነበር። ለዚህም ነው የቃል ኪዳኑ ታቦት የነበረበትን
ያን ስፍራ መጽሐፍ ቅዱስ “የመገናኛው ድንኳን” ብሎ የሚጠራው። የመገናኛው ድንኳን የእግዚአብሔር ሕዝብ እንደ ማህበር በአምላካቸው
ፊት የሚገኙበት ስፍራ ነበር። ቤተ መቅደሱን ቅዱስ የሚያደርገው ስፍራው በጌታ አምላክ መገኘት ስር መሆኑ ነበር። በቤተ መቅደስ
ከመገኘት ባሻገር ደግሞ እያንዳንዱ እስራኤላዊና በመካከላቸውም የሚኖር መጻተኛ ሁሉ በልቡና በቤቱ እግዚአብሔርን ማምለክና ማክበር
ነበረበት። ክግብጽ ባርነት ጌታ ነጻ ያወጣቸውና የራሳቸው የሆነ ምድር የሰጣቸው ምክንያት በነጻነት ከእርሱ ጋር እንዲኖሩበት ነበር።
የበረከቱ ምንጭ የከነዓን ምድር በምድር ካሉ ሌሎች ስፍራዎች ሁሉ የተለየና ያማረ መሆኑ ሳይሆን፣ ጌታ አምላክ ራሱ የሚጎበኘው ምድር
መሆኑ ነበር። ዛሬ በአዲስ ኪዳን ዘመን ያለን ክርስቲያኖችም እንዲሁ በገዛ ራሱ ደሙ የዋጀንን እና የዘለዓለምን ሕይወት የሰጠንን
ጌታ የምናመልከው በቤተ ክርስቲያንና በህብረት ብቻ ሳይሆን በግላችን፣ በአእምሮአችን፣ በሰውነታችን፣ በስሜታችንና በማንነታችን ሁሉ
ነው። ፈርጀ ብዙ በሆነው በግል ኑሮአችን እንዲሁም በቤተሰባችን እና በግንኙነቶቻችን ሁሉ መካከል እርሱን ማክበርና ደስ የሚያሰኘውን
ለማድረግ መትጋት እንዳለብን እንዲህ ሲል መጽሐፍ ቅዱስ ያስተምረናል ያዝዘናልም፤
“ብልቶቻችሁ
ዓመፃ ሊያደርጉ ለርኩስነትና ለዓመፃ ባሪያዎች አድርጋችሁ እንዳቀረባችሁ እንደዚሁ ብልቶቻችሁ ሊቀደሱ ለጽድቅ ባሪያዎች አድርጋችሁ
አሁን አቅርቡ።” ሮሜ 6፡19
“እንግዲህ እንደ እግዚአብሔር ምርጦች ቅዱሳን ሆናችሁ የተወደዳችሁም ሆናችሁ፣ ምሕረትን ርኅራኄን፣
ቸርነትን፣ ትሕትናን፣ የዋህነትን፣ ትዕግሥትን ልበሱ፣እርስ በርሳችሁ ትዕግሥትን አድርጉ፣ ማንም በባልንጀራው ላይ የሚነቅፈው ነገር
ካለው ይቅር ተባባሉ፣ ክርስቶስ ይቅር እንዳላችሁ እናንተ ደግሞ እንዲህ አድርጉ፣ በእነዚህም ሁሉ ላይ የፍጻሜ ማሰሪያ የሆነውን
ፍቅርን ልበሱት። በአንድ አካልም የተጠራችሁለት ደግሞ የክርስቶስ ሰላም በልባችሁ ይግዛ። የምታመሰግኑም ሁኑ፣ የእግዚአብሔር ቃል
በሙላት ይኑርባችሁ፣ በጥበብ ሁሉ እርስ በርሳችሁ አስተምሩና ገስፁ፣ በመዝሙርና በዝማሬ በመንፈሳዊም ቅኔ በጸጋው በልባችሁ ለእግዚአብሔር
ዘምሩ፣ እግዚአብሔርን በእርሱ እያመሰገናችሁ በቃል ቢሆን ወይም በሥራ የምታደርጉትን ሁሉ በጌታ በኢየሱስ ስም አድርጉት።” ቆላስይስ 3፡12-17
ጌታን
ኢየሱስ ክርስቶስን ስንቀበል በመንፈስ ቅዱስ ኃይል ከእግዚአብሔር ዳግም ተወልደናል፣ ስለዚህ አዲስ ፍጥረቶች ነን። ኃጢዓት ካመጣብን
የዘለዓለም ሞት ድነናል፣ ስለዚህም በክርስቶስ ጽድቅ ምክንያት ጻድቃን ሆነናል። በዓመጻችን ምክንያት ተጣልተነውና ተለይተነው ከነበረው
ከአምላካችን ከእግዚአብሔር ጋር በክርስቶስ ደም ታርቀናል፣ ስለዚህም የእግዚአብሔር ልጆች ነን። ይገዛን ከነበረውና ዛሬም የማያምነውን
ዓለም ከሚገዛው ከጨለማው ገዥ ከዲያብሎስ፣ ከጭፍሮቹና ከአጋንንት ስልጣን ነጻ ወጥተን ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ የፍቅር መንግሥት ፈልሰናል፣
በጨለማው ገዥና በሥርዓቱም ሁሉ ላይ ሥልጣን ተሰጥቶናል። ኢየሱስ
ክርስቶስ በክብር ሲገለጽ እኛም ደግሞ ከእርሱ ጋር በክብር እንድንገለጥና አብረነው በሕይወት እንድንነግስ ታጭተናል። እነዚህን እውነቶች
ሁሉ እንዳንረሳ፣ እንዳንደክምና እንዳንታክት፣ ወደ እውነት ሁሉ እንዲመራንና ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ያደረገልንን እና ያስተማረንን
የሚያስታውሰንን መንፈስ ቅዱስን እንደ ርስታችን መያዣ ተቀብለናል (ዮሐ 1፡12-13 ዮሐንስ
3፡16-18 ሮሜ 5፡1-2 ሮሜ 6፡6 2ኛ ቆሮ 5፡17 ቆላስይስ 1፡13-14 ሉቃስ 10፡19-20) በዚህ ሁሉ እውነት
ለተከበብን ክርስቲያኖች ነው ታዲያ ሐዋርያው ጳውሎስ “እንደ ተወደዱ ልጆች
እግዚአብሔርን የምትከተሉ ሁኑ” የሚለን። ልጆች በብዙ መንገድ
ወላጆቻቸውን እንደሚመስሉ ሁሉ እኛም በክርስቶስ ከእግዚአብሔር ዳግም የተወለድን ክርስቲያኖች ዳግም የወለደንን እግዚአብሔርን እንድንመስል
ይጠበቅብናል። ይህ ምን ማለት እንደሆነ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ሲያስተምር እንዲህ ብሎአል፡
“እናንተ ስለነገርኋችሁ ቃል ቃል አሁን ንጹሐን ናችሁ፣ በእኔ ኑሩ እኔም በእናንተ። ቅርንጫፍ
በወይኑ ግንድ ባይኖር ከራሱ ፍሬ ሊያፈራ እንዳይቻለው እንዲሁ እናንተ ደግሞ በእኔ ባትኖሩ አትችሉም። እኔ የወይን ግንድ ነኝ እናንተም
ቅርንጫፎች ናችሁ። ያለ እኔ ምንም ልታደርጉ አትችሉምና፣ በእኔ የሚኖር እኔም በእርሱ፣እርሱ ብዙ ፍሬ ያፈራል። ....ብዙ ፍሬ
ብታፈሩና ደቀ መዛሙርቴ ብትሆኑ በዚህ አባቴ ይከበራል።” ዮሐንስ
ወንጌል 15፡3-8
ስለ
ወደደንና ስላዳነን የምንወደውን እግዚአብሔርን ደስ ለማሰኘት ክርስቲያኖች ሁሉ እንፈልጋለን። እንዴት ደስ እንደምናሰኘው ግን ብዙ
ጥያቄዎችና ግራ መጋባት ሊኖርብን ይችላል።በእርግጥ ጌታ አምላካችንን ደስ የምናሰኝባቸው በመጽሐፍ ቅዱስ የተገለጡልን ብዙ መንገዶች
ቢኖሩም እነዚያ ነገሮች ሁሉ በሁለት ዋና ዋና ምሰሶዎች ተጠቃልለዋል። እነዚያ ሁለት ምሰሶዎች ደግሞ በብሉይ ኪዳን በሙሴ በኩል
ተገልጠው በአዲስ ኪዳን ደግሞ ጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ ለደቀ መዛሙርቱ ያስተማራቸው ናቸው፤ 1ኛ) እግዚአብሔርን አምላካችንን
በፍጹም ልባችን፣ በፍጹምም ነፍሳችን፣ በፍጹምም ኃይላችን መውደድ (ዘዳግም 6፡4-9) እና 2ኛ) ባልንጀራችንን (ሌላውን ሰው ሁሉ) እንደ ራሳችን መውደድ (ዘሌዋውያን 19፡18)
ናቸው (ማቴዎስ 22፡37) ።
የዚህ
የዛሬው መልእክት ትኩረት የመጀመሪያው ትዕዛዝ ነው። እግዚአብሔር አምላካችንን በእርግጥ የምንወደው ከሆነ በማንኛውም ስፍራ፣ ጊዜና
ሁኔታ ውስጥ እንከተለዋለን፣ እንታዘዘዋለን፣ ደስ የሚያሰኘውንም ለማወቅና ለማድረግ እንተጋለን። ጌታን የምንከተለው ቤተ ክርስቲያን
ስንሄድ፣ ከክርስቲያኖች ጋር ህብረት ስናደርግ፣ ለሌሎች ሰዎች ስንመሰክር፣ ስንሰብክና ስናስተምር ብቻ ሳይሆን ለብቻችንም ስንሆን፣
በቤታችን ውስጥ፣ በስራ ቦታችን፣ በመንገድ ላይ፣ በሰዎች መካከል፣ በሃሳቦቻችንና በምርጫዎቻችን ሁሉ ውስጥ ሊሆን ይገባል። እንደ
ፍቅር ጠንካራ ነገር የለም። እግዚአብሔር በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ለእኛ የገለጠው ፍቅር ደግሞ የፍቅሮች ሁሉ ቁንጮና መሰረት
ነው። አንዳንዶቻችን “ታዲያ እንዴት ይሆን ለጌታ ያለኝን ፍቅር ልገልጽ የምችለው” ብለን ልናስብ እንችላለን። እንድንከተለውና ደቀ
መዛሙርቱ እንድንሆን የጠራን ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ እንዴት እንደምንከተለውም በግልጽ አስተምሮአል። ሐዋርያትና ደቀ መዛሙርትም ከጌታ
የተማሩትን መሰረት በማድረግ ስለዚሁ በብዙ መንገድ አስተምረውናል።
በቆላስይስ
መልእክት ላይ ከተጻፈውና ከላይ ከተጠቀሰው ክፍል እንደምንመለከተው ለእግዚአብሔር የሚታዘዙና እርሱን ደስ በሚያሰኝ ሕይወት ለመኖር
የሚሹ ሁሉ ሊከታተሏቸው፣ ሊያደርጓቸውና ሊሆኗቸው ከሚገቡት ነገሮች መካከል ጥቂቶቹን ለናሙና ያህል እንመልከት፡
1)
ልንቀደስና በቅድስና
ልንኖር ያስፈልጋል። መቀደስ ማለት በአንድ በኩል በዓለም ካለውና ለእግዚአብሔር ተገቢውን ቦታ ከማይሰጥ ከንቱና የኃጢአት የኑሮ
ዘይቤ መለየትና መሸሽ ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ አምላካችንን ለማወቅ፣ ሃሳቡን ለመረዳትና ለመታዘዝ እንድንችል ወደ እርሱ መቅረብ
ማለት ነው። ተቀደሱ ብሎ ያዘዘን አምላክ የሚቀድሰንም እርሱ ራሱ መሆኑን አስተምሮናል። “ዳሩ ግን እኔ ቅዱስ ነኝና ቅዱሳን ሁኑ ተብሎ ስለ ተጻፈ የጠራችሁ ቅዱስ እንደሆነ እናንተ
ደግሞ በኑሮአችሁ ሁሉ ቅዱሳን ሁኑ፣ ለሰው ፊትም ሳያደላ በእያንዳንዱ ላይ እንደ ሥራው የሚፈርደውን አባት ብላችሁ ብትጠሩ በእንግድነታችሁ
ዘመን በፍርሃት ኑሩ።” 1ኛ ጴጥሮስ 1፡15-17 “እኔ የምቀድሳችሁ
እግዚአብሔር ነኝ” ዘሌዋውያን 20፡8
2)
አንዱ ክርስቲያን
ከሌላው ክርስቲያን ጋርም ሆነ ገና ጌታን ካላወቁ ሰዎች ጋር በሚኖሩት ግንኙነቶች ሁሉ በተቻለው መጠን በምሕረት፣ በርኅራኄ፣ በቸርነት፣
በትሕትና፣ በየዋህነትና፣ በትዕግሥት ሊኖር ያስፈልጋል። አለመግባባትን የሚፈጥሩ ሁኔታዎች እንዳይፈጠሩ በእኛ በኩል በተቻለን ሁሉ
መጣር፣ ከተፈጠሩ ደግሞ የምንሰጠው ምላሽ፣ አስተያየትም ሆነ ነቀፌታ፣ የማንስማማውንም ሰው ቢሆን በክርስቲያንነቱ ወይም በሰውነቱ
የሚያክብር፣ በጸጋና በትህትና የተሞላ መሆን አለበት። እንዲህ ተብሎ ተጽፎአልና፡
“የተጠራችሁለት ለዚህ ነውና፣ ክርስቶስ ደግሞ ፍለጋውን እንድትከተሉ ምሳሌ ትቶላችሁ ስለ እናንተ
መከራን ተቀብሎአልና። እርሱ ኃጢዓት አላደረገም፥ ተንኮልም በአፉ አልተገኘበትም፣ ሲሰድቡት መልሶ አልተሳደበም፣ መከራንም ሲቀበል
አልዛተም፥ ነገር ግን በጽድቅ ለሚፈርደው ራሱን አሳልፎ ሰጠ።” 1ኛ
ጴጥሮስ 2፡21-23
3)
እግዚአብሔር
አምላካችንን በትክክል ልናውቀው የምንችለው ቃሉን ስናነብ፣ ስናጠና፣ ስናሰላስል፣ ስንረዳውና ስንታዘዘው ነው። ጌታ መንፈስ ቅዱስም
በግልና በህብረት በሕይወታችን በሙላት ሊሰራና በሰማያዊ ነገሮች ሁሉ ፍሬያማ ሊያደርገን የሚችለው የእግዚአብሔርን ቃል በየጊዜውና
በሰፊው ስንመገብ ነው። ስለዚህ በግላችን መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብና ማጥናት ያስፈልገናል። ከሌሎች ክርስቲያኖች ጋር በሕብረት የሚደረጉት
የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቶችና በቤተ ክርስቲያን የሚሰጡት ትምህርቶች ወይም ስብከቶች አስፈላጊ ቢሆኑም ለብቻቸው ግን በቂ አይደሉም።
በመንፈሳዊ ሕይወታችን እንደሚገባን ለማደግና ፍሬያማ ክርስቲያን ለመኖን ከፈለግን በቂ ጊዜ ሰጥተን ቃሉን ማንበብና ማጥናት የግድ
አስፈላጊ ነው። ቪዲዮ ማየት፣ በኢንተርኔት የሚቀርቡ መልእክቶችን መስማትና በሌሎች ክርስቲያኖች የተጻፉ መጻህፍትን ማንበብ ሁሉ
ጠቃሚ ናቸው። እነዚህ ሁሉ ግን እኛ ራሳችን በቀጥታ መጽሐፍ ቅዱስን ማንበባችንን እና ማጥናታችንን ሊተኩ አይገባም። ንጉስ ዳዊት
“አንተን እንዳልበድል ቃልህን በልቤ ሰወርሁ።” ይላል (መዝሙር 118፤11 ) ጌታ ኢየሱስ ራሱ ደግሞ በማቴዎስ ወንጌል ላይ እንዲህ ሲል ለአይሁድ
መሪዎች ተናገረ፡ “መጻሕፍትንና የእግዚአብሔርን ኃይል አታውቁምና
ትስታላችሁ።” ማቴዎስ 22፡29
4)
በምንም ሁኔታ
ውስጥ ብንሆን የእግዚአብሔር ሰላም በልባችን ውስጥ እንዲገዛ ራሳችንን ለመንፈስ ቅዱስ አመራር ዝግጁ ማድረግና እርሱን ማዳመጥ ያስፈልጋል።
ይህን ልናደርግ የምንችለው ከአምላካችን ጋር የምንሆንበትን ጊዜ ወስነን ስናመሰግን፣ ስናመልክና ስንጸልይ ለሌሎችም ስናማልድ ነው።
ጌታ አምላክ ከልጆቹ ጋር መነጋገር ይናፍቃል። በክርስቶስ በማመን ዳግም የተወለደ ሁሉ ወደ እግዚአብሔር በመቅረብ የመጸለይ፣ በነጻነት
የማምለክና እርሱን የማክበር መብትና ልዩ እድል አለው። አምላካችን ማልደን ስንፈልገው፣ ወደ እርሱም ቀርበን በምስጋና በተሞላ ልብ ደስታችንንም ሆነ ሸክማችንን
በጸሎትና በዝማሬ በፊቱ ስናቀርብ ደስ ይለዋል። እንዴት ማምለክና መጸለይ እንደምንችል ባይገባን እንኳን ፈቃዳችንን ለእርሱ ካስገዛን
መንፈስ ቅዱስ ራሱ ይረዳናል በእኛም ውስጥ ሆኖ ይቃትትልናል፣ ለሌሎችም ይማልዳል። “እንዲሁም ደግሞ መንፈስ ድካማችንን ያግዛል እንዴት እንድንጸልይ እንደሚገባን አናውቅምና፣
ነገር ግን መንፈስ ራሱ በማይነገር መቃተት ይማልድልናል፣ ልብንም የሚመረምረው የመንፈስ አሳብ ምን እንደሆነ ያውቃል፣ እንደ እግዚአብሔር
ፈቃድ ስለ ቅዱሳን ይማልዳልና።” ሮሜ 8፡26-27
ዓይን ያላየውንና ጆሮ ያልሰማውን ወደ
ሰውም ሃሳብ ሊገባ የማይችለውን ድንቅ የሆነ የዘለዓለም ክብር አዘጋጅቶ በገዛ ራሱ ፈቃድና ጽድቅ በክርስቶስ ዳግም የወለደንን አምላካችንን
ለመምሰል መናፈቅ በእውነት ዳግም የተወለደ ክርስቲያን ሁሉ ባህርይ ነውና ቃሉ እንደሚያዝዘን እንደ ተወደዱ ልጆች እግዚአብሔርን
እንምሰል፣ እርሱን እንከተል።